በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

የወጣቶች ጥያቄ

ወላጆቼ እምነት እንዲጥሉብኝ ምን ላድርግ?

ወላጆቼ እምነት እንዲጥሉብኝ ምን ላድርግ?

 ማወቅ የሚኖርብህ ነገር

 ወላጆችህ እምነት የሚጥሉብህ በዚህ ረገድ ከዚህ ቀደም ያተረፍከውን ስም መሠረት በማድረግ ነው። ወላጆችህ ያወጧቸውን መመሪያዎች ማክበር የባንክ ዕዳ እንደ መክፈል ነው። ወላጆችህን በታዘዝክ ማለትም ‘ዕዳህን’ በከፈልክ ቁጥር ተጨማሪ ብድር (ነፃነት) የማግኘት አጋጣሚህ ሰፊ ይሆናል። በሌላ በኩል ደግሞ እምነት የሚጣልብህ ሰው ካልሆንክ ወላጆችህ የሚሰጡህን ‘ብድር’ ቢቀንሱ ልትገረም አይገባም።

 የወላጆችህን አመኔታ ለማትረፍ ጊዜ ያስፈልጋል። ወላጆችህ ተጨማሪ ነፃነት የሚሰጡህ፣ ኃላፊነት የሚሰማህ ሰው መሆንህን በሚገባ ካስመሠከርክ ነው።

 እውነተኛ ታሪክ፦ “በአሥራዎቹ ዕድሜ ሳለሁ ወላጆቼ ምን እንደሚጠብቁብኝ በደንብ አውቅ ነበር፤ ስለዚህ እነሱ የሚፈልጉትን ነገር የማደርግ እያስመሰልኩ በድብቅ ግን እኔ የፈለግኩትን ነገር አደርግ ነበር። ይህም ወላጆቼ በእኔ ላይ እምነት እንዳይጥሉ አደረጋቸው። ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ግን፣ ተጨማሪ ነፃነት ለማግኘት አቋራጭ መንገድ እንደሌለና ሐቀኛ አለመሆን እንደማያዋጣ ተገነዘብኩ። የወላጆችህን አመኔታ ማትረፍ ከፈለግህ እምነት የሚጣልብህ ዓይነት ሰው መሆን አለብህ።”—ክሬግ

 ምን ማድረግ ትችላለህ?

 አስቸጋሪ በሚሆንብህ ጊዜም እንኳ እውነቱን ተናገር። ሁሉም ሰው ስህተት ይሠራል፤ ሆኖም ስህተትህን ለመደበቅ የምትዋሽ ከሆነ (አሊያም በቂ መረጃ ባለመስጠት እውነታውን አዛብተህ የምታቀርብ ከሆነ) የወላጆችህን አመኔታ ጨርሶ ታጣለህ። በሌላ በኩል ግን እውነታውን አንድም ሳታዛባ ሁልጊዜ የምትናገር ከሆነ ወላጆችህ ለስህተቶችህ ኃላፊነት የምትወስድ ሰው መሆንህንና መብሰልህን ያስተውላሉ። እንዲህ ያለ ሰው ደግሞ እምነት ይጣልበታል።

 “ስህተት መሥራትህ እምነት የማይጣልብህ ሰው እንድትሆን የሚያደርገው ሁልጊዜ አይደለም፤ ስህተቶችህን ለመደበቅ የምትሞክር ከሆነ ግን ምንጊዜም ቢሆን የሌሎችን አመኔታ ማጣትህ አይቀርም።”—አና

 መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “በሁሉም ነገር በሐቀኝነት ለመኖር እንፈልጋለን።”—ዕብራውያን 13:18

  •   ሊታሰብባቸው የሚገቡ ነጥቦች፦ ወላጆችህ የት እንደምትሄድና ምን እንደምታደርግ ሲጠይቁህ አንድም ሳትደብቅ እውነቱን ትነግራቸዋለህ? ወይስ ወላጆችህ የት ሄደህ እንደነበረና ምን ስታደርግ እንደነበር ሲጠይቁህ አንዳንድ ነገሮች ሸፋፍነህ ታቀርባለህ?

 ኃላፊነት የሚሰማው ሰው ሁን። ወላጆችህ የሚያወጧቸውን ሁሉንም መመሪያዎች ታዘዝ። የተሰጡህን ሥራዎች ወዲያውኑ አከናውን። ቀጠሮ አክባሪ ሁን። ትምህርት ቤት የሚሰጥህን የክፍልና የቤት ሥራ ማንም ሳያስታውስህ ሥራ። በተባልከው ሰዓት ቤት ግባ።

 “ወላጆችህ ከጓደኞችህ ጋር እስከ 3:00 ተዝናንተህ ወደ ቤት እንድትመለስ ቢፈቅዱልህ እስከ 4:30 ድረስ አታምሽ፤ በሰዓትህ ካልገባህ በሚቀጥለው ጊዜ ከጓደኞችህ ጋር ለመዝናናት እንዲፈቅዱልህ መጠበቅ የለብህም!”—ራያን

 መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “እያንዳንዱ የራሱን የኃላፊነት ሸክም ይሸከማል።”—ገላትያ 6:5

  •   ሊታሰብበት የሚገባ ነጥብ፦ ሰዓት በማክበር፣ የተሰጡህን ሥራዎች በማከናወን እንዲሁም የማትወዳቸውን መመሪያዎች እንኳ በመታዘዝ ረገድ ምን ዓይነት ስም አትርፈሃል?

 ትዕግሥተኛ ሁን። የወላጆችህን አመኔታ የሚያሳጣህ ነገር ካደረግክ አመኔታቸውን መልሶ ለማግኘት ጊዜ ይወስዳል። እስከዚያው ድረስ በትዕግሥት ጠብቅ።

 “ዕድሜዬ ከፍ ሲል ወላጆቼ የበለጠ ኃላፊነት ስላልሰጡኝ ተበሳጭቼ ነበር። ዕድሜ በመጨመርና የበሰለ ሰው በመሆን መካከል ልዩነት እንዳለ አልተገነዘብኩም። ወላጆቼን፣ እምነት የሚጣልብኝ ሰው መሆኔን የማሳይበት አጋጣሚ እንዲሰጡኝ ጠየቅኳቸው። ትንሽ ጊዜ ቢወስድብኝም ያሰብኩት ተሳክቶልኛል። ደግሞም አንድን ሰው እምነት እንዲጣልበት የሚያደርገው ዕድሜው መጨመሩ ሳይሆን ድርጊቱ እንደሆነ ተረድቻለሁ።”—ሬቸል

 መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “በምታደርገው ነገር ታማኝ መሆንህን [አሳይ]።”—3 ዮሐንስ 5

  •   ሊታሰብበት የሚገባ ነጥብ፦ ወላጆችህ እምነት እንዲጥሉብህ (በአንተ ላይ እምነት አጥተው ከነበረ እንደገና አመኔታቸው ለማግኘት) ‘ታማኝ ሰው መሆንህን ለማሳየት’ ልታደርጋቸው የምትችላቸው አንዳንድ ነገሮች የትኞቹ ናቸው?

 ጠቃሚ ምክር፦ ሰዓት ከማክበር፣ የተሰጡህን ሥራዎች ከማከናወን፣ በተባልከው ሰዓት ቤት ከመግባት አሊያም ከሌሎች ነገሮች ጋር በተያያዘ ግብ አውጣ። ወላጆችህ ቁርጥ ውሳኔህን እንዲያውቁ አድርግ፤ በተጨማሪም እንዲተማመኑብህ ምን እንድታደርግ እንደሚፈልጉ ጠይቃቸው። ከዚያም ‘ከቀድሞ አኗኗራችሁ ጋር የሚስማማውን አሮጌውን ስብዕናችሁን አውልቃችሁ ጣሉ’ የሚለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ምክር በተግባር ለማዋል ከፍተኛ ጥረት አድርግ። (ኤፌሶን 4:22) በጊዜ ሂደት ወላጆችህ የምታደርገውን መሻሻል ማስተዋላቸው አይቀርም!