በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

የወጣቶች ጥያቄ

ትኩረቴን መሰብሰብ የምችለው እንዴት ነው?

ትኩረቴን መሰብሰብ የምችለው እንዴት ነው?

 ትኩረቴን መሰብሰብ የሚከብደኝ ለምንድን ነው?

 “እንደ ድሮው መጽሐፍ አላነብም። አሁን አሁንማ ረጅም አንቀጽ እንኳ ማንበብ አልፈልግም።”—ኢሌይን

 “አንድ ቪዲዮ እንደተንዛዛ ከተሰማኝ ወደፊት አሳልፈዋለሁ።”—ሚራንዳ

 “አስፈላጊ ነገር ላይ ትኩረት አድርጌ ሳለ ስልኬ ከጮኸ፣ የማስበው ‘ማነው የጻፈልኝ?’ የሚለውን ብቻ ነው።”—ጄን

 ቴክኖሎጂ ትኩረት መሰብሰብ ከባድ እንዲሆንብን ሊያደርግ ይችላል? አንዳንዶች እንደዚያ ይሰማቸዋል። ደራሲና የማኔጅመንት አማካሪ የሆኑት ኒኮላስ ካር እንዲህ በማለት ጽፈዋል፦ “ኢንተርኔት ይበልጥ በተጠቀምን መጠን አንጎላችን ትኩረቱ እንዲከፋፈል እያሠለጠንነው እንሄዳለን፤ አንድን መረጃ በፍጥነትና ውጤታማ በሆነ መንገድ እንዲቀበል ሆኖም ረዘም ላለ ጊዜ ማተኮር እንዲከብደው እናደርገዋለን።” a

 ቴክኖሎጂ ትኩረትህን መሰብሰብ ከባድ እንዲሆንብህ የሚያደርግባቸውን ሦስት ሁኔታዎች እንመልከት።

  •   ከሌሎች ጋር ስታወራ። ማሪያ የተባለች አንዲት ወጣት እንዲህ ብላለች፦ “ብዙዎች ከሰዎች ጋር እያወሩ የጽሑፍ መልእክት ይላላካሉ፤ ጌም ይጫወታሉ ወይም ስልካቸው ላይ ማኅበራዊ ሚዲያ ይጠቀማሉ፤ ለሚያነጋግሩት ሰው ሙሉ ትኩረታቸውን አይሰጡትም።”

  •   ክፍል ውስጥ። ዲጂታል ኪድስ የተባለው መጽሐፍ እንደገለጸው “አብዛኞቹ ተማሪዎች ክፍል ውስጥ በኤሌክትሮኒክ መሣሪያዎቻቸው ይጻጻፋሉ፣ ኢንተርኔት ይጠቀማሉ ወይም ቪዲዮ ያያሉ”፤ የኤሌክትሮኒክ መሣሪያቸውን የሚጠቀሙበት “ከትምህርት ጋር ለተያያዘ ጉዳይ አይደለም።”

  •   በጥናት ወቅት። የ22 ዓመቱ ክሪስ “ስልኬ ምልክት ባሳየ ቁጥር ለማየት በጣም እፈተናለሁ” ብሏል። ተማሪ ከሆንክ በኤሌክትሮኒክ መሣሪያዎችህ ትኩረትህ ሲከፋፈል የአንድ ሰዓት የቤት ሥራ ሦስት ሰዓት ወይም ከዚያ በላይ ሊፈጅብህ ይችላል።

 ሊታሰብበት የሚገባው ነገር፦ ቴክኖሎጂ ትኩረትህን እንዲከፋፍለውና እንዲቆጣጠርህ ከፈቀድክ ትኩረትህን መሰብሰብ ይከብድሃል።

ትኩረቱ የተከፋፈለ አእምሮ እንዳልተገራ ፈረስ ነው፤ እሱ ይቆጣጠርሃል እንጂ አንተ አትቆጣጠረውም

 ትኩረቴን ለመሰብሰብ ምን ይረዳኛል?

  •   ከሌሎች ጋር ስታወራ። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “ስለ ራሳችሁ ፍላጎት ብቻ ከማሰብ ይልቅ እያንዳንዳችሁ ለሌሎች ሰዎች ፍላጎትም ትኩረት ስጡ።” (ፊልጵስዩስ 2:4) በጥሞና በማዳመጥ አሳቢነት አሳይ። ግለሰቡን ዓይን ዓይኑን እያየህ አነጋግረው፤ እንዲሁም የኤሌክትሮኒክ መሣሪያዎችህ ትኩረትህን እንዲከፋፍሉብህ አትፍቀድ።

     “ከሰዎች ጋር ስታወራ በየመሃሉ ስልክህን ላለመመልከት ራስህን ተቆጣጠር። ለምታነጋግረው ሰው ሙሉ ትኩረትህን በመስጠት እንደምታከብረው አሳይ።”—ቶማስ

     ጠቃሚ ምክር፦ ከሰዎች ጋር ስትነጋገር ስልክህን ከአካባቢው አርቅ። ተመራማሪዎች እንደሚገልጹት ስልክህ ካጠገብህ መሆኑ ብቻ ትኩረትህን ሊሰርቀው ይችላል፤ ምክንያቱም በማንኛውም ሰዓት ሊያቋርጥህ እንደሚችል ታውቃለህ።

  •   ክፍል ውስጥ። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “እንዴት እንደምታዳምጡ በጥሞና አስቡ።” (ሉቃስ 8:18) ትምህርት ቤትህ፣ ክፍል ውስጥ ኢንተርኔት እንድትጠቀም የሚፈቅድልህ ከሆነ በትምህርትህ ላይ ማተኮር ባለብህ ሰዓት መልእክቶችን ባለማየት፣ ጌም ባለመጫወት ወይም ቻት ባለማድረግ ይህን ምክር በሥራ ላይ ማዋል ትችላለህ።

     “ክፍል ውስጥ በትኩረት ለማዳመጥ ጥረት አድርግ። ማስታወሻ ያዝ። ትኩረትህን የሚከፋፍል ነገር እንዳያጋጥምህ ከተቻለ ከፊት ተቀመጥ።”—ኬረን

     ጠቃሚ ምክር፦ ኮምፒውተር ከመጠቀም ይልቅ ወረቀት ላይ ማስታወሻ ጻፍ። አንዳንድ ጥናቶች እንደሚያሳዩት እንዲህ ማድረግ ትኩረትህን ለመሰብሰብና የተማርከውን ነገር ለማስታወስ ያግዝሃል።

  •   በጥናት ወቅት። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “ጥበብን አግኝ፤ ማስተዋልንም አዳብር።” (ምሳሌ 4:5) እንዲህ ማድረግ የምትችለው ፈተና ለማለፍ ብቻ ትምህርቱን ገረፍ ገረፍ በማድረግ ሳይሆን በጥልቀት በማሰብ ነው።

     “ሳጠና ታብሌቴን የአውሮፕላን ሞድ ላይ በማድረግ ጥናቴ ላይ ብቻ አተኩራለሁ። የሚመጡልኝን መልእክቶች አላይም። ማስታወስ የምፈልገው ነገር ካለ እጽፈዋለሁ።”—ክሪስ

     ጠቃሚ ምክር፦ የምታጠናበት ቦታ ትኩረት ለመሰብሰብ የሚያመች እንዲሆን አድርግ። ቦታው ንጹሕና ያልተዝረከረከ ይሁን።

a ዘ ሻሎውስ—ዋት ዚ ኢንተርኔት ኢዝ ዱዊንግ ቱ አወር ብሬንስ ከተባለው መጽሐፍ የተወሰደ።