በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

እንደ እኔ ዓይነት ፆታ ያለው ሰው ይማርከኛል—ግብረ ሰዶማዊ ነኝ ማለት ነው?

እንደ እኔ ዓይነት ፆታ ያለው ሰው ይማርከኛል—ግብረ ሰዶማዊ ነኝ ማለት ነው?

 አይደለም!

 እውነታው፦ ተመሳሳይ ፆታ ባላቸው ሰዎች መካከል የሚፈጠረው የፍቅር ስሜት በአብዛኛው ጊዜያዊ እንጂ ዘላቂ አይደለም።

 ሊዜት የምትባል የ16 ዓመት ወጣት በዚህ ትስማማለች፤ ሊዜት በአንድ ወቅት አንዲት ሴት ወድዳ ነበር። እንዲህ ብላለች፦ “በባዮሎጂ ክፍለ ጊዜ፣ በጉርምስና ዕድሜ ላይ የሆርሞን መጠን በጣም ሊለዋወጥ እንደሚችል ተማርኩ። ወጣቶች ስለ ሰውነታቸው በደንብ ቢያውቁ ኖሮ ተመሳሳይ ፆታ ካለው ሰው ጋር የሚይዛቸው ፍቅር ጊዜያዊ ሊሆን እንደሚችል መገንዘባቸው ስለማይቀር ግብረ ሰዶማዊ ለመሆን አይነሳሱም።”

ሁሉም ወጣቶች በፊታቸው ሁለት ምርጫ ተቀምጦላቸዋል፦ ፆታን በተመለከተ በዓለም ላይ የሚታየውን ያዘቀጠ አመለካከት መቀበል ወይም በአምላክ ቃል ውስጥ የሚገኘውን ላቅ ያለ የሥነ ምግባር ጎዳና መከተል

 ይሁን እንጂ የሚሰማህ ነገር ከጊዜያዊ ስሜት ይበልጥ ሥር የሰደደ እንደሆነ የምታስብ ቢሆንስ? እንደ ራሱ ዓይነት ፆታ ላለው ሰው የፍቅር ስሜት የሚያድርበትን ሰው ከግብረ ሰዶም እንዲርቅ አምላክ ማዘዙ ጭካኔ ነው?

 ጭካኔ እንደሆነ የሚሰማህ ከሆነ አንድ ነገር ልብ ልትል ይገባል፤ እንዲህ ያለው አመለካከት የመነጨው ሰዎች የፆታ ስሜታቸውን ከማርካት ወደኋላ ማለት የለባቸውም ከሚለው የተሳሳተ አስተሳሰብ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ፣ ሰዎች ተገቢ ላልሆኑ የፆታ ፍላጎቶች ላለመሸነፍ ከልባቸው እስከፈለጉ ድረስ ከእነዚህ ነገሮች መራቅ እንደሚችሉ ማረጋገጫ በመስጠት አምላክ የሰው ልጆችን እንዳከበራቸው ይገልጻል።—ቆላስይስ 3:5

 በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የሚገኘው መመሪያ ምክንያታዊነት የጎደለው አይደለም። የአምላክ ቃል ግብረ ሰዶማዊ ለሆኑም ሆነ ላልሆኑ ሰዎች “ከዝሙት ሽሹ” የሚል አንድ ዓይነት መመሪያ ይሰጣል። (1 ቆሮንቶስ 6:18) ደግሞም ከመጽሐፍ ቅዱስ የሥነ ምግባር መሥፈርቶች ጋር ተስማምተው መኖር የሚፈልጉ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ግብረ ሰዶማዊ ያልሆኑ ሰዎች ምንም ዓይነት ፈተና ቢያጋጥማቸውም ራሳቸውን ገዝተው መኖር ችለዋል። የግብረ ሰዶማዊነት ዝንባሌ ያላቸው ሰዎችም ቢሆኑ አምላክን ለማስደሰት ከልባቸው የሚፈልጉ ከሆነ እንዲሁ ማድረግ ይችላሉ።—ዘዳግም 30:19