በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ክፍል 7

ልጃችሁን ማሠልጠን የምትችሉት እንዴት ነው?

ልጃችሁን ማሠልጠን የምትችሉት እንዴት ነው?

“ዛሬ የማዝህን እነዚህን ትእዛዛት በልብህ ያዝ፤ በልጆችህም ውስጥ ቅረጻቸው።”—ዘዳግም 6:6, 7

ይሖዋ ቤተሰብን ሲመሠርት ለወላጆች ልጆቻቸውን የመንከባከብ ኃላፊነት ሰጥቷቸዋል። (ቆላስይስ 3:20) ወላጆች፣ ልጆቻችሁ ይሖዋን እንዲወዱና ሲያድጉ ኃላፊነት የሚሰማቸው ሰዎች እንዲሆኑ የማሠልጠን ኃላፊነት አለባችሁ። (2 ጢሞቴዎስ 1:5፤ 3:15) በተጨማሪም በልጆቻችሁ ልብ ውስጥ ያለውን ነገር ለማወቅ ጥረት ማድረግ ይኖርባችኋል። እርግጥ ነው፣ የእናንተ ምሳሌነትም በጣም አስፈላጊ ነው። የይሖዋን ቃል ለልጆቻችሁ ጥሩ አድርጋችሁ ማስተማር የምትችሉት ቃሉ መጀመሪያ በእናንተ ልብ ውስጥ ካለ ነው።—መዝሙር 40:8

1 ልጆቻችሁ እናንተን ማዋራት ቀላል እንዲሆንላቸው አድርጉ

መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል? ‘ለመስማት የፈጠናችሁና ለመናገር የዘገያችሁ ሁኑ።’ (ያዕቆብ 1:19) ልጆቻችሁ ከእናንተ ጋር በነፃነት ማውራት እንደሚችሉ እንዲሰማቸው ማድረግ እንደምትፈልጉ የታወቀ ነው። እንግዲያው ማውራት ሲፈልጉ ለማዳመጥ ዝግጁ መሆናችሁን እንዲያውቁ አድርጉ። ሐሳባቸውን በነፃነት መግለጽ ቀላል እንዲሆንላቸው በቤታችሁ ውስጥ ሰላማዊ ሁኔታ መኖር አለበት። (ያዕቆብ 3:18) የምትቆጧቸው ወይም የምትኮንኗቸው ከመሰላቸው የልባቸውን በግልጽ ላይነግሯችሁ ይችላሉ። ስለዚህ ልጆቻችሁን ታገሷቸው፤ እንዲሁም እንደምትወዷቸው አዘውትራችሁ ንገሯቸው።—ማቴዎስ 3:17፤ 1 ቆሮንቶስ 8:1

ምን ማድረግ ትችላላችሁ?

  • ልጆቻችሁ ማውራት ሲፈልጉ ጆሮ ሰጥታችሁ አዳምጧቸው

  • ችግሮች በሚኖሩበት ጊዜ ብቻ ሳይሆን አዘውትራችሁ ከልጆቻችሁ ጋር ተጨዋወቱ

2 ምን ለማለት እንደፈለጉ ለመረዳት ጥረት አድርጉ

መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል? “አንድን ነገር ጠለቅ ብሎ የሚያስተውል ሰው ስኬታማ ይሆናል።” (ምሳሌ 16:20) አንዳንድ ጊዜ፣ ልጆቻችሁ ምን ለማለት እንደፈለጉ በትክክል ለመረዳት ከተናገሩት ነገር በስተጀርባ ያለውን ለማወቅ መጣር ይኖርባችኋል። ወጣቶች ነገሮችን አጋንነው ማውራታቸው ወይም በልባቸው የሌለውን ነገር መናገራቸው የተለመደ ነው። “እውነታውን ከመስማቱ በፊት መልስ የሚሰጥ ሰው፣ ሞኝነት ይሆንበታል።” (ምሳሌ 18:13) ስለዚህ ልጆቻችሁ በሚናገሩት ነገር ቶሎ አትቆጡ።—ምሳሌ 19:11

ምን ማድረግ ትችላላችሁ?

  • ልጆቻችሁ የሚናገሩት ምንም ሆነ ምን፣ በመሃል ላለማቋረጥ ወይም ላለመቆጣት ጥረት አድርጉ

  • እናንተ በእነሱ ዕድሜ ሳላችሁ ምን ይሰማችሁ እንደነበር እንዲሁም ትልቅ ቦታ ትሰጡት የነበረውን ነገር ለማስታወስ ሞክሩ

3 አንድ አቋም ይኑራችሁ

መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል? “ልጄ ሆይ፣ የአባትህን ተግሣጽ አዳምጥ፤ የእናትህንም መመሪያ አትተው።” (ምሳሌ 1:8) ይሖዋ በልጆች ላይ ሥልጣን የሰጠው ለአባትም ለእናትም ነው። ልጆቻችሁ እንዲያከብሯችሁና እንዲታዘዟችሁ ልታስተምሯቸው ይገባል። (ኤፌሶን 6:1-3) ወላጆች “በአስተሳሰብ . . . ፍጹም አንድነት” ከሌላቸው ልጆች ይህን ማስተዋል ይችላሉ። (1 ቆሮንቶስ 1:10) በአንድ ጉዳይ ላይ ሁለታችሁ ካልተስማማችሁ ልዩነታችሁን ልጆቻችሁ እንዳያዩ ጥረት አድርጉ፤ ምክንያቱም እነሱ ፊት መጋጨታችሁ ለእናንተ ያላቸው አክብሮት እንዲቀንስ ሊያደርግ ይችላል።

ምን ማድረግ ትችላላችሁ?

  • ለልጆቻችሁ ተግሣጽ ስለምትሰጡበት መንገድ ሁለታችሁ ተወያይታችሁ ተስማሙ

  • ልጆቻችሁን ስለምታሠለጥኑበት መንገድ በመካከላችሁ የሐሳብ ልዩነት ካለ የትዳር ጓደኛችሁን አመለካከት ለመረዳት ጥረት አድርጉ

4 ዕቅድ አውጡ

መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል? “ልጅን ሊሄድበት በሚገባው መንገድ አሠልጥነው።” (ምሳሌ 22:6) ልጆቻችሁን ጥሩ አድርጋችሁ ልታሠለጥኑ የምትችሉት እንዲያው በአጋጣሚ አይደለም። ልጆቻችሁን እንዴት እንደምታሠለጥኑ ዕቅድ ማውጣት ያስፈልጋችኋል፤ ሥልጠናው ተግሣጽ መስጠትንም ያካትታል። (መዝሙር 127:4፤ ምሳሌ 29:17) ተግሣጽ መስጠት ሲባል መቅጣት ማለት ብቻ ሳይሆን ልጃችሁ አንድ መመሪያ የተሰጠው ለምን እንደሆነ እንዲገነዘብ መርዳትን ይጨምራል። (ምሳሌ 28:7) በተጨማሪም ልጆቻችሁ የይሖዋን ቃል እንዲወዱና መመሪያዎቹን እንዲያስተውሉ አሠልጥኗቸው። (መዝሙር 1:2) ይህም ጤናማ ሕሊና እንዲያዳብሩ ይረዳቸዋል።—ዕብራውያን 5:14

ምን ማድረግ ትችላላችሁ?

  • ልጆቻችሁ አምላክን ሊተማመኑበት የሚችሉ እውን አካል እንደሆነ አድርገው እንዲያዩት አድርጉ

  • ልጆቻችሁ በኢንተርኔትና በማኅበራዊ ድረ ገጾች ላይ ሊያጋጥሟቸው የሚችሉትን የሥነ ምግባር አደጋዎች ለይተው ማወቅ እንዲችሉና ከአደጋዎቹ እንዲርቁ እርዷቸው። የፆታ ጥቃት ለመፈጸም ከሚያደቡ ሰዎች መራቅ የሚችሉት እንዴት እንደሆነም አስተምሯቸው

“ልጅን ሊሄድበት በሚገባው መንገድ አሠልጥነው”