በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

መቻቻል—መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?

መቻቻል—መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?

 “ሰላም ሊሰፍን የሚችለው መቻቻል ካለ ብቻ ነው።”—የዩኔስኮ የመቻቻል መርሆች መግለጫ፣ 1995

 በተቃራኒው ግን አለመቻቻል በሰዎች ልብ ውስጥ ንቀት ከዚያም አልፎ ጥላቻ እንዲዘራ ያደርጋል። ብዙውን ጊዜ እንዲህ ያሉት ስሜቶች ወደ ጥላቻ ንግግር፣ አድልዎና የኃይል ድርጊት ያመራሉ።

 ይሁን እንጂ ሰዎች መቻቻልን የሚረዱበት መንገድ የተለያየ ነው። አንዳንዶች መቻቻል ሲባል ‘ማንኛውም ዓይነት ድርጊትና ባሕርይ ትክክል ነው’ ብሎ መቀበል ማለት እንደሆነ ይሰማቸዋል። ሌሎች ግን በዚህ ረገድ የመጽሐፍ ቅዱስ ዓይነት አመለካከት አላቸው፤ መቻቻል ማለት፣ እነሱ ራሳቸው አንዳንድ እሴቶችና እምነቶች ትክክል እንዳልሆኑ ቢያምኑም እንኳ ሌሎች በዚህ ረገድ የራሳቸውን ምርጫ የማድረግ መብት እንዳላቸው ማክበር እንደሆነ ይረዳሉ።

 ታዲያ መጽሐፍ ቅዱስ በዘመናዊው ዓለም በሚኖሩ ሰዎች መካከል መቻቻል እንዲሰፍን ሊረዳ ይችላል?

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተገለጸው መቻቻል መሠረቱ ምንድን ነው?

 መጽሐፍ ቅዱስ መቻቻልን ያበረታታል። “ምክንያታዊነታችሁ በሰው ሁሉ ዘንድ የታወቀ ይሁን” ይላል። (ፊልጵስዩስ 4:5) መጽሐፍ ቅዱስ ለሌሎች አሳቢነትና አክብሮት እንድናሳይ እንዲሁም በተገቢው መንገድ እንድንይዛቸው ያበረታታናል። ይህን ምክር ተግባራዊ የሚያደርጉ ሰዎች የሌላውን ሰው እሴት አይቀበሉት ወይም አይመሩበት ይሆናል፤ ሆኖም ግለሰቡ በመረጠው መንገድ ቢመላለስ አይቃወሙትም።

 መጽሐፍ ቅዱስ መቻቻልን ቢያበረታታም አምላክ ለሰዎች ያስቀመጠው መሥፈርት እንዳለ ይገልጻል። “ሰው ሆይ፣ [አምላክ] መልካም የሆነውን ነግሮሃል” ይላል። (ሚክያስ 6:8) ሰዎች የተሻለ ሕይወት መምራት እንዲችሉ አምላክ የሰጣቸው መመሪያ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሰፍሯል።—ኢሳይያስ 48:17, 18

 አምላክ በሌሎች ላይ የመፍረድ ሥልጣን አልሰጠንም። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “ሕግ የሚሰጥና የሚፈርድ አንድ ብቻ ነው፤ . . . በባልንጀራህ ላይ የምትፈርድ አንተ ማን ነህ?” (ያዕቆብ 4:12) አምላክ ለእያንዳንዳችን የራሳችንን ምርጫ የማድረግ ነፃነት ሰጥቶናል፤ ለምናደርገው ምርጫ ኃላፊነቱን የምንወስደውም ራሳችን ነን።—ዘዳግም 30:19

መጽሐፍ ቅዱስ ለሌሎች አክብሮት ስለማሳየት ምን ይላል?

 መጽሐፍ ቅዱስ “ሰውን ሁሉ አክብሩ” ይላል። (1 ጴጥሮስ 2:17 የ1980 ትርጉም) ስለዚህ በመጽሐፍ ቅዱስ መሥፈርቶች የሚመሩ ሰዎች ሁሉንም ሰው ያከብራሉ፤ ሰዎቹ የሚያምኑበት ነገር ወይም የሚከተሉት አኗኗር ምንም ይሁን ምን አክብሮት ከማሳየት ወደኋላ አይሉም። (ሉቃስ 6:31) ይህ ማለት ግን በመጽሐፍ ቅዱስ የሚመሩ ሰዎች ማንኛውንም ዓይነት እምነት ወይም አመለካከት ይቀበላሉ አሊያም ሌሎች የሚያደርጉትን ማንኛውንም ዓይነት ውሳኔ ይደግፋሉ ማለት አይደለም። ያም ቢሆን ሌሎችን አክብሮት በሌለው ወይም ጨዋነት በጎደለው መንገድ አይዙም። ከዚህ ይልቅ ኢየሱስ ሌሎችን የያዘበትን መንገድ ለመኮረጅ ጥረት ያደርጋሉ።

 አንድ ምሳሌ እንመልከት፦ በአንድ ወቅት ኢየሱስ እሱ የማይደግፈውን ሃይማኖት የምትከተልን አንዲት ሴት አነጋግሮ ነበር። ሴትየዋ ባሏ ካልሆነ ሰው ጋር ትኖር ነበር፤ ይህም ቢሆን ኢየሱስ የማይደግፈው ዓይነት አኗኗር ነው። እንደዚያም ሆኖ ግን ሴትየዋን ያነጋገራት በአክብሮት ነበር።—ዮሐንስ 4:9, 17-24

 እንደ ኢየሱስ ሁሉ ክርስቲያኖችም ሊያዳምጧቸው ፈቃደኛ ለሆኑ ሰዎች ሁሉ እምነታቸውን ለማስረዳት ዝግጁ ናቸው፤ ይህን የሚያደርጉት ግን “ጥልቅ አክብሮት” በሚንጸባረቅበት መንገድ ነው። (1 ጴጥሮስ 3:15) መጽሐፍ ቅዱስ ክርስቲያኖች አመለካከታቸውን በሌሎች ላይ መጫን እንደሌለባቸው ያሳስባል። የክርስቶስ ተከታይ ‘ሊጣላ እንደማይገባው ከዚህ ይልቅ ለሰው ሁሉ ገር መሆን’ እንዳለበት ይናገራል፤ ይህ ከእሱ የተለየ እምነት ያላቸውን ሰዎችም ይጨምራል።—2 ጢሞቴዎስ 2:24

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ጥላቻ ምን ይላል?

 “ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ለመኖር ጥረት [እንድናደርግ]” ይመክረናል። (ዕብራውያን 12:14) ከሰዎች ጋር በሰላም ለመኖር ጥረት የሚያደርግ ሰው ጥላቻን ማስወገድ አለበት። ከሚያምንባቸው ነገሮች ጋር የሚጋጭ ነገር ሳያደርግ፣ ከሌሎች ጋር በሰላም ለመኖር አቅሙ የፈቀደውን ያህል ይጥራል። (ማቴዎስ 5:9) እንዲያውም መጽሐፍ ቅዱስ፣ ክርስቲያኖች ጠላቶቻቸውን እንዲወዱ ማለትም መጥፎ ነገር የሚያደርጉባቸውን ሰዎች በደግነት እንዲይዙ ያበረታታል።—ማቴዎስ 5:44

 እርግጥ ነው፣ መጽሐፍ ቅዱስ ሰዎችን የሚያዋርዱና በሌሎች ላይ ጉዳት የሚያደርሱ ድርጊቶችን አምላክ ‘እንደሚጠላ’ ወይም ‘እንደሚጸየፍ’ ይናገራል። (ምሳሌ 6:16-19) ሆኖም እዚህ ላይ መጥላት የሚለው ቃል የተሠራበት መጥፎ ድርጊቶች በአምላክ ዘንድ ፈጽሞ ተቀባይነት እንደሌላቸው ለማመልከት ነው። አምላክ አኗኗራቸውን ለመቀየርና በእሱ መሥፈርቶች መሠረት ለመኖር ፈቃደኛ የሆኑ ሰዎችን ይቅር እንደሚላቸውና ሊረዳቸው ፈቃደኛ እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል።—ኢሳይያስ 55:7

ስለ መቻቻል እና መከባበር የሚገልጹ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች

 ቲቶ 3:2 “ምክንያታዊ እንዲሆኑና ለሰው ሁሉ ገርነትን በተሟላ ሁኔታ እንዲያንጸባርቁ አሳስባቸው።”

 ምክንያታዊ የሆነ ሰው የተለያየ አመለካከት ያላቸውን ሰዎች በገርነት ይይዛል፤ ይህም በሰዎች መካከል መከባበር እንዲሰፍን አስተዋጽኦ ያደርጋል።

 ማቴዎስ 7:12 “ሰዎች እንዲያደርጉላችሁ የምትፈልጉትን ነገር ሁሉ እናንተም አድርጉላቸው።”

 ሁላችንም ብንሆን ሌሎች በአክብሮት ሲይዙን እንዲሁም አመለካከታችንንና ስሜታችንን ግምት ውስጥ ሲያስገቡ ደስ ይለናል። ኢየሱስ ያስተማረውን ይህን ታዋቂ የሥነ ምግባር መመሪያ እንዴት ተግባራዊ ማድረግ እንደምትችል ለማወቅ “ወርቃማው ሕግ ምንድን ነው?” የሚለውን ርዕስ አንብብ።

 ኢያሱ 24:15 “የምታገለግሉትን ዛሬውኑ ምረጡ።”

 ሌሎች የራሳቸውን ምርጫ ለማድረግ ያላቸውን መብት ስናከብርላቸው ሰላም እንዲሰፍን አስተዋጽኦ እናደርጋለን።

 የሐዋርያት ሥራ 10:34 ‘አምላክ አያዳላም።’

 አምላክ የሰዎችን ባሕል፣ ፆታ፣ ዜግነት፣ ዘር ወይም አስተዳደግ ተመልክቶ አድልዎ አያደርግም። አምላክን መምሰል የሚፈልጉ ለሁሉም ሰዎች አክብሮት ያሳያሉ።

 ዕንባቆም 1:12, 13 ‘አምላክ ክፋትን ዝም ብሎ ማየት አይችልም።’

 አምላክ መቻቻልን ቢያበረታታም ትዕግሥቱ ገደብ አለው። ክፋት ለዘላለም እንዲቀጥል አይፈቅድም። ስለዚህ ጉዳይ ይበልጥ ለማወቅ አምላክ መከራ እንዲኖር የፈቀደው ለምንድን ነው? የሚለውን ቪዲዮ ተመልከት።

 ሮም 12:19 “‘በቀል የእኔ ነው፤ እኔ ብድራትን እመልሳለሁ’ ይላል ይሖዋ” ተብሎ ስለተጻፈ [ለአምላክ] ቁጣ ዕድል ስጡ።” a

 ይሖዋ ለማንኛውም ሰው፣ የበቀል እርምጃ የመውሰድ ሥልጣን አልሰጠም። እሱ በወሰነው ጊዜ ፍትሐዊ እርምጃ ይወስዳል። ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት “ሰዎች ፍትሕ ለማግኘት የሚያሰሙት ጩኸት ተሰሚነት ያገኝ ይሆን?” የሚለውን ርዕስ አንብብ።

a ይሖዋ የአምላክ የግል ስም ነው። (መዝሙር 83:18) “ይሖዋ ማን ነው?” የሚለውን ርዕስ ተመልከት።