በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

ኢየሱስ የተወለደው መቼ ነው?

ኢየሱስ የተወለደው መቼ ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?

 ቀጥሎ የቀረቡት የማመሳከሪያ ሥራዎች እንደሚያሳዩት መጽሐፍ ቅዱስ ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደበትን ቀን አይናገርም፦

  •   “ክርስቶስ የተወለደበት ትክክለኛ ቀን አይታወቅም።”—ኒው ካቶሊክ ኢንሳይክሎፒዲያ

  •   “ክርስቶስ የተወለደበት ትክክለኛ ቀን አይታወቅም።”—ኢንሳይክሎፒዲያ ኦቭ ኧርሊ ክርስቺያኒቲ

 መጽሐፍ ቅዱስ ‘ኢየሱስ የተወለደው መቼ ነው?’ ለሚለው ጥያቄ ቀጥተኛ መልስ ባይሰጥም ብዙዎች ኢየሱስ የተወለደው በታኅሣሥ 29 (ወይም እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ታኅሣሥ 25) እንዳልሆነ እንዲያምኑ ያደረጓቸውን በኢየሱስ ልደት ወቅት የነበሩ ሁለት ነገሮችን ይጠቅሳል።

በቅዝቃዜ ወቅት አይደለም

  1.   የሕዝብ ቆጠራ። ኢየሱስ ከመወለዱ ትንሽ ቀደም ብሎ አውግስጦስ ቄሳር “የዓለም ሕዝብ ሁሉ እንዲመዘገብ አዋጅ አወጣ።” እያንዳንዱ ሰው “ወደየራሱ ከተማ” በመሄድ መመዝገብ ይጠበቅበት ነበር፤ ይህም ለአንድ ሳምንት ወይም ከዚያ በላይ ጉዞ ማድረግን ይጠይቅ ይሆናል። (ሉቃስ 2:1-3) ይህ ትእዛዝ የወጣው ግብር ለመሰብሰብ ወይም ወታደሮችን ለመመልመል ታስቦ ሊሆን ይችላል፤ አዋጁ የወጣው መቼም ይሁን መቼ፣ አብዛኛው ሕዝብ እንዲህ ያለ ጉዞ ማድረግ እንደማይፈልግ ግልጽ ነው። በመሆኑም አውግስጦስ በቅዝቃዜው ወቅት እንዲህ ያለ ጉዞ እንዲያደርጉ የሚያስገድድ አዋጅ በማውጣት አብዛኛውን ሕዝብ የሚያስቆጣ ድርጊት እንደማይፈጽም የታወቀ ነው።

  2.   በጎች። በዚያን ወቅት “ሌሊት ሜዳ ላይ መንጎቻቸውን ሲጠብቁ የሚያድሩ እረኞች ነበሩ።” (ሉቃስ 2:8) ዴይሊ ላይፍ ኢን ዘ ታይም ኦቭ ጂሰስ የተባለው መጽሐፍ “ከፋሲካ በዓል [የመጋቢት አጋማሽ] በፊት ካለው ሳምንት አንስቶ እስከ ኅዳር አጋማሽ ድረስ” መንጋዎች ሜዳ ላይ ያድሩ እንደነበር ተናግሯል። አክሎም እንዲህ ብሏል፦ “መንጋዎቹ ክረምቱን የሚያሳልፉት በጉሮኗቸው ውስጥ ሆነው ነበር። እረኞች መንጋቸውን ሲጠብቁ በሜዳ ማደራቸውን ከሚናገረው የወንጌል ዘገባ አንጻር ሲታይ የገና በዓል ቅዝቃዜ በሚበረታባቸው ወራት መከበሩ ራሱ ቀኑ ፈጽሞ ትክክል እንዳልሆነ ያስገነዝባል።”

በመጸው መግቢያ

 ኢየሱስ ከሞተበት ከኒሳን 14 ቀን 33 ዓ.ም. የጸደይ ወቅት ተነስተን ወደ ኋላ በመቁጠር የተወለደበትን ወቅት መገመት እንችላለን። (ዮሐንስ 19:14-16) ኢየሱስ ሦስት ዓመት ተኩል የፈጀውን አገልግሎቱን ሲጀምር 30 ዓመቱ ገደማ ነበር፤ ስለዚህ የተወለደው በ2 ዓ.ዓ. በነበረው የመጸው መግቢያ ላይ ነበር ማለት ይቻላል።—ሉቃስ 3:23

ገና ታኅሣሥ 29 የሚከበረው ለምንድን ነው?

 ኢየሱስ በታኅሣሥ 29 (ወይም እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ታኅሣሥ 25) መወለዱን የሚያሳይ መረጃ ከሌለ ገና በዚህ ወቅት የሚከበረው ለምንድን ነው? ኢንሳይክሎፒዲያ ብሪታኒካ እንደሚናገረው የቤተ ክርስቲያን መሪዎች በቅዝቃዜው ወቅት መገባደጃ ላይ ያለውን ይህን ቀን የመረጡት “‘ድል የማትደረገው ፀሐይ የልደት ቀን’ ከሚከበርበት የሮማውያን አረማዊ ክብረ በዓል ጋር እንዲገጣጠም ፈልገው” ስለነበረ ይመስላል። ኢንሳይክሎፒዲያ አሜሪካና እንደሚናገረው ከሆነ ይህ የተደረገው “ከአሕዛብ ለመጡ ሰዎች ክርስትና ይበልጥ ማራኪ እንዲሆን ታስቦ” እንደሆነ አብዛኞቹ ምሁራን ያምናሉ።