በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

ታላቁ መከራ ምንድን ነው?

ታላቁ መከራ ምንድን ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?

 ታላቁ መከራ፣ እስከ ዛሬ በሰው ልጆች ላይ ከደረሱት መከራዎች ሁሉ ይበልጥ አስጨናቂ ጊዜ ይሆናል። የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢት እንደሚናገረው፣ ይህ የሚሆነው “በመጨረሻዎቹ ቀናት” ወይም ‘በፍጻሜው ዘመን’ ነው። (2 ጢሞቴዎስ 3:1፤ ዳንኤል 12:4) በዚያ ወቅት “ከአምላክ የፍጥረት ሥራ መጀመሪያ አንስቶ እስከዚያ ጊዜ ድረስ ሆኖ የማያውቅ ዳግመኛም የማይሆን መከራ ይከሰታል።”—ማርቆስ 13:19፤ ዳንኤል 12:1፤ ማቴዎስ 24:21, 22

በታላቁ መከራ ወቅት የሚፈጸሙ ክንውኖች

  •   የሐሰት ሃይማኖት ይጠፋል። የሐሰት ሃይማኖት በአስደናቂ ፍጥነት ይጠፋል። (ራእይ 17:1, 5፤ 18:9, 10, 21) በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የተወከሉት የፓለቲካ ኃይሎች፣ የሐሰት ሃይማኖትን በማጥፋት የአምላክን ፈቃድ ይፈጽማሉ።—ራእይ 17:3, 15-18 a

  •   በእውነተኛው ሃይማኖት ላይ ጥቃት ይሰነዘራል። ሕዝቅኤል በተመለከተው ራእይ ላይ ‘በማጎግ ምድር የሚገኘው ጎግ’ በሚል መጠሪያ የተገለጹት ግንባር የፈጠሩ ብሔራት፣ እውነተኛውን ሃይማኖት የሚከተሉ ሰዎችን ለመደምሰስ ይነሳሉ። ሆኖም አምላክ አገልጋዮቹን ከጥፋት ይታደጋቸዋል።—ሕዝቅኤል 38:1, 2, 9-12, 18-23

  •   በምድር ነዋሪዎች ላይ ፍርድ ይበየናል። ኢየሱስ በሰው ልጆች ሁሉ ላይ ፍርድ የሚበይን ሲሆን “እረኛ በጎቹን ከፍየሎቹ እንደሚለይ ሁሉ እሱም ሰዎችን አንዱን ከሌላው ይለያል።” (ማቴዎስ 25:31-33) በሰዎቹ ላይ ለሚበየነው ፍርድ መሠረት የሚሆነው፣ ከኢየሱስ ጋር በሰማይ ለሚገዙት ‘ወንድሞቹ’ ድጋፍ መስጠታቸው ወይም አለመስጠታቸው ነው።—ማቴዎስ 25:34-46

  •   የአምላክ መንግሥት ገዢዎች ይሰበሰባሉ። ከክርስቶስ ጋር ሆነው እንዲገዙ የተመረጡ ታማኝ ሰዎች ምድራዊ ሕይወታቸውን ሲያጠናቅቁ ትንሣኤ አግኝተው ወደ ሰማይ ይሄዳሉ።—ማቴዎስ 24:31፤ 1 ቆሮንቶስ 15:50-53፤ 1 ተሰሎንቄ 4:15-17

  •   አርማጌዶን። “ሁሉን ቻይ በሆነው አምላክ ታላቅ ቀን” የሚካሄደው ይህ ጦርነት “የይሖዋ ቀን” በመባልም ይታወቃል። (ራእይ 16:14, 16፤ ኢሳይያስ 13:9፤ 2 ጴጥሮስ 3:12) ክርስቶስ የጥፋት ፍርድ የሚበይንባቸው በሙሉ ይጠፋሉ። (ሶፎንያስ 1:18፤ 2 ተሰሎንቄ 1:6-10) ከሚጠፉት መካከል በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሰባት ራስ ባለው አውሬ የተመሰለው ዓለም አቀፍ የፖለቲካ ሥርዓት ይገኝበታል።—ራእይ 19:19-21

ከታላቁ መከራ በኋላ የሚፈጸሙ ክንውኖች

  •   ሰይጣንና አጋንንቱ ይታሰራሉ። አንድ ታላቅ መልአክ፣ ሰይጣንንና አጋንንቱን “ወደ ጥልቁ” ይወረውራቸዋል፤ ወደ “ጥልቁ” መጣላቸው የሞቱ ያህል ከእንቅስቃሴ ውጭ እንደሚሆኑ ያመለክታል። (ራእይ 20:1-3) ሰይጣን ወደ ጥልቁ ሲወረወር የሚኖረውን ሁኔታ እስር ቤት ከመግባት ጋር ማመሳሰል ይቻላል፤ በየትኛውም ቦታ በሚፈጸሙ ክንውኖች ላይ ተጽዕኖ ማሳደር አይችልም።—ራእይ 20:7

  •   የሺው ዓመት ግዛት ይጀምራል። የአምላክ መንግሥት የ1,000 ዓመት ግዛቱን የሚጀምር ሲሆን በዚህ ወቅት ለሰው ልጆች ብዙ በረከቶችን ያመጣል። (ራእይ 5:9, 10፤ 20:4, 6) ቁጥሩ ያልተገለጸ “እጅግ ብዙ ሕዝብ” “ታላቁን መከራ” በሕይወት አልፎ በምድር ላይ የሺው ዓመት ግዛት ሲጀምር ለማየት ይበቃል።—ራእይ 7:9, 14፤ መዝሙር 37:9-11

a በራእይ መጽሐፍ ውስጥ የሐሰት ሃይማኖት፣ ታላቂቱ ባቢሎን እና “ታላቂቱ አመንዝራ” ተብሎ ተገልጿል። (ራእይ 17:1, 5) ታላቂቱ ባቢሎንን የሚያጠፋው ደማቅ ቀይ አውሬ፣ አንድን ዓለም አቀፋዊ ድርጅት ይወክላል፤ የዚህ ድርጅት ዓላማ የዓለምን መንግሥታት ማስተባበርና መወከል ነው። ይህ ድርጅት በመጀመሪያ የመንግሥታት ቃል ኪዳን ማኅበር ይባል የነበረ ሲሆን በአሁኑ ወቅት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ተብሏል።