በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በፖሊሶች ታጅቦ መስበክ

በፖሊሶች ታጅቦ መስበክ

 የይሖዋ ምሥክር ከሆንክ፣ ከቤት ወደ ቤት ምሥራቹን ስትሰብክ በፖሊሶች ብትታጀብ ምን ይሰማሃል? በማይክሮኔዥያ የሚኖረው ጆሴፍ በ2017 እንዲህ ያለ ሁኔታ አጋጥሞት ነበር። ጆሴፍና ሌሎች ሦስት የይሖዋ ምሥክሮች ራቅ ብለው በሚገኙ ደሴቶች ውስጥ ለሚኖሩ ሰዎች ለመስበክ በተደረገ ልዩ ዘመቻ ላይ እየተካፈሉ ነበር።

 ቀትር አካባቢ አራቱ የይሖዋ ምሥክሮች 600 ገደማ ነዋሪ ወዳላት አንዲት ደሴት ደረሱ። የይሖዋ ምሥክሮቹ በባሕሩ ዳርቻ ላይ የደሴቲቱን ከንቲባ አገኙት። ጆሴፍ ቀጥሎ የሆነውን ሲናገር እንዲህ ብሏል፦ “ከንቲባው በፖሊስ መኪና ወደ ሁሉም ቤቶች መሄድ እንደምንችል ነገረን። ያቀረበልን ግብዣ አስገርሞን ነበር፤ ሆኖም እንደማንፈልግ በአክብሮት ነገርነው። እንደለመድነው በእግራችን ከቤት ወደ ቤት እየሄድን ሰዎችን ማነጋገር ፈልገን ነበር።”

 የይሖዋ ምሥክሮቹ የቻሉትን ያህል ብዙ ሰው ለማነጋገር ቆርጠው በእግራቸው መጓዝ ጀመሩ። እንዲህ ብለዋል፦ “ሰዎቹ እንግዳ ተቀባይ ነበሩ፤ እንዲሁም መልእክታችንን ለመስማት ፍላጎት ነበራቸው። በመሆኑም በእያንዳንዱ ቤት ካሰብነው በላይ ብዙ ቆየን።”

 ቀኑ እየገፋ ሲሄድ የፖሊስ መኪናው ሁለት ጊዜ ጆሴፍን አለፈውና በሦስተኛው ላይ ቆመ። ፖሊሶቹ ጆሴፍን ወደቀሩት ቤቶች ሊያደርሱት እንደሚችሉ ነገሩት። እንዲህ ብሏል፦ “እንደማልፈልግ ነገርኳቸው። እነሱ ግን ‘ብዙ ሰዓት የለህም፤ ስለዚህ ወደቀሩት ቤቶች እንውሰድህ’ አሉኝ። ገና ብዙ ቤቶች ቀርተውኝ ስለነበር እንቢ ልላቸው አልቻልኩም። ወደ እያንዳንዱ ቤት ስንደርስ ፖሊሶቹ የቤቱን ባለቤት ስም ይነግሩኝ ነበር፤ እንዲሁም በሩን ሳንኳኳ የሚከፍትልኝ ሰው ካላገኘሁ የመኪናቸውን ጥሩንባ ነፍተው ሰዎቹን እንደሚጠሩልኝ ነገሩኝ።

 “በእነሱ እርዳታ በዚያ ቀን ሁሉንም ቤት ማዳረስ ችለናል። ብዙ ጽሑፎች አበረከትን፤ እንዲሁም ፍላጎት ያሳዩ ሰዎችን ተመልሰን ለመጠየቅ ዝግጅት አደረግን።”

 ፖሊሶቹ ለጆሴፍ “ምሥራች ማዳረስ በመቻላችን በጣም ደስ ብሎናል” አሉት። የይሖዋ ምሥክሮቹ ምሽት ላይ ደሴቲቱን ለቀው ሲሄዱ ፖሊሶቹ ባሕሩ ዳርቻ ላይ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጽሑፎች በእጃቸው ይዘው በፈገግታ እጃቸውን እያውለበለቡ ተሰናበቷቸው።